“ዛሬ ኢትዮጵያውያንን ሁሉ የሚያኮራ ታሪካዊ ሁነት ተፈጽሟል፡፡ የሁለት አሻጋሪ ፕሮጀክቶች መሠረት ድንጋ አስቀምጠናል፡፡” ጠቅላይ ሚንስትር አብይ አህመድ (ዶ/ር)

 

“ዛሬ ኢትዮጵያውያንን ሁሉ የሚያኮራ ታሪካዊ ሁነት ተፈጽሟል፡፡ የሁለት አሻጋሪ ፕሮጀክቶች መሠረት ድንጋ አስቀምጠናል፡፡” ጠቅላይ ሚንስትር አብይ አህመድ (ዶ/ር)

መስከረም 22/2018 (ኢዜአ)፦

አዲስ አበባ፤

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የዩሪያ ማዳበሪያ እና የጎዴ ነዳጅ ማጣሪያ ፋብሪካዎች ግንባታ የመሰረት ድንጋይ አስቀመጡ፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት ዛሬ ለኢትዮጵያዊያን ሁሉ የሚያኮራ ታሪካዊ ሁነት ተፈፅሟል፤ የሁለት አሻጋሪ ፕሮጀክቶች የመሠረት ድንጋይ አስቀምጠናል ብለዋል።

የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግ ከዳንጎቴ ግሩፕ ጋር በመተባበር የሚገነባው የዩሪያ ማዳበሪያ ፋብሪካ እና በጎልደን ኮንኮርድ ግሩፕ የሚገነባው የጎዴ ነዳጅ ማጣሪያ ፋብሪካ መሠረት ድንጋይ መቀመጡን ጠቁመዋል።

የጎዴ ነዳጅ ማጣሪያ ከሂላል የነዳጅ ስፍራ ድፍድፍ ነዳጅ በማውጣት፣ በማጣራትና በማጠራቀም በአመት 3 ነጥብ 5 ሚሊዮን ቶን የማምረት አቅም ያለው ነው ብለዋል።

በሌላ በኩልም የማዳበሪያ ፋብሪካው ከካሉብ የጋዝ ስፍራ በማውጣት እና 108 ኪሎሜትር የማጓጓዣ ቱቦ በመጠቀም በአመት 3 ሚሊዮን ቶን አምርቶ ለገበያ እንደሚያቀርብ ጠቁመዋል።

ፕሮጀክቶቹ የኢንዱስትሪ እድገትን ከማሳየት በላይ ናቸው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ እድሎቻችንን የመጠቀም፣ ትብብሮችን የማጠናከር እና ሰላምን የማጽናት የጋራ ኃላፊነታችንን የሚያሳዩ ናቸው ሲሉም ገልጸዋል።

ጠቅላይ ሚኒስትሩ ኢትዮጵያዊያን ሁሉ በኅብረት እና በአንድነት ለእድገት መሰባሰባችንን አጠናክረን እንድንቀጥል ሲሉ ጥሪያቸውን አቅርበዋል።

ይኽን ስናደርግ እውነተኛውን የኢትዮጵያዊ ማንነት መንፈስ በሚያከብር መንገድ በአለም መድረክ የኢትዮጵያን ስፍራ ከፍ እናደርጋለን ብለዋል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በመልዕክታቸው።